Sparital photo

Edu sory about this ok i am not image any thing ok did you forgive me plssss you must sis because it is not prepacked from you mean not saying excuse so we can continue as it is 10q have a nice time
አሥራ ሦስቱ ሕማማተ መስቀል
በሰሙነ ሕማማት ጠቅለል ባለ መልኩ የምናስባቸው የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሕማማት አሥራ ሦስት ናቸው፡፡ እነርሱም አሥራ ሦስቱ ሕማማተ መስቀል ይባላሉ፡፡ ለክርስቲያኖች እነዚህን ሕማማተ መስቀል ማወቅና ዘወትር ማሰብ ተገቢ በመሆኑ እንደሚከተለው ቀርበዋል፡፡

1.     ተኰርዖተ ርእስ (ራስና በዘንግ መመታት)

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን በዘንግ መመታቱንና መቀጥቀጡን የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ተኰርዖት›› የሚለው ቃል ኩርዐ - መታ ከሚለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ነው፡፡ ርእስ ደግሞ ራስ ማለት ነው፡፡ አገረ ገዥው ጲላጦስ ‹‹እኔ ከዚህ ጻድቅ ሰው ደም ንጹሕ ነኝ›› ብሎ እጁን ከታጠበ በኋላ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ገርፎ ለካህናት አለቆችና ለሽማግሎች አሳልፎ ሰጥቶት ነበር፡፡ በአይሁድ ሕግ የተገረፈ አይሰቀልም፤ የሚሰቀል ደግሞ አይገረፍም፡፡ እርሱ ጲላጦስ ግን ከገረፈው በኋላ፣ የበደል በደል፣ እንዲሰቅሉት አሳልፎ ሰጣቸው (ማቴ 27-24፤ ማር 15-15፤ ሉቃ 23-25፤ ዮሐ 18-39)፡፡

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተላልፎ ከተሰጠ በኋላ የእሾህ አክሊል ጐንጉነው ራሱ ላይ ደፍተውበታል፡፡ ራሱንም በዘንግ መትተውታል (ማር 15-19)፡፡ የሰው ዘር ከአዳም ጀምሮ በጠላቱ በዲያብሎስ በተጐነጐነ የኃጢአት እሾህ ራሱ ተይዞ ነበርና ይህንኑ ለማስወገድ ከሰማይ የወረደ ሰማያዊ የሆነ ዳግማዊ አዳም ክርስቶስ በጠላቶቹ በአይሁድ ተንኮል የተጐነጐነ አክሊለ ሦክ እንደ ዘውድ ደፋ፡፡ በሲኦል ወድቆ በዲያብሎስ ተረግጦ ራሱ የሚቀጠቀጠውን የሰውን ልጅ ለማዳን መድኃኔዓለም ክርስቶስ ራሱን በመቃ ተቀጠቀጠ፡፡ ከራሱ ላይ በሚወርደው ደም ፊቱ ተሸፈነ፡፡
 
2.     ተፀፍዖ መልታሕት (በጥፊ መመታት)


አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ እጃቸው በደም፣ ጣቶቻቸው በበደል በረከሰ በአይሁድ እጅ በጥፊ መመታቱን የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ተፀፍዖ›› የሚለው ቃል ፀፍዐ በጥፊ መታ ከሚለው የግእዝ ግሥ የወጣ ነው፡፡ መልታሕት ደግሞ ፊት ጉንጭ ማለት ነው፡፡

ጌታችን ለሊቀ ካህናት ቀያፋ እውነትን መናገር እንደ ስድብ ተቆጥሮበት መላልሰው ፊቱን በጥፊ መትተውታል፡፡ ፊቱንም በጨርቅ ሸፍነው ‹‹ክርስቶስ ሆይ በጥፊ የመታህ ማነው? ትንቢት ተናገርልን›› እያሉ ዘብተውበታል፡፡ በጠላት ዲያብሎስ እጅ ወድቆ በነፍሱ ይቀለድበትና ይንገላታ የነበረውን የሰውን ልጅ ለማዳን ብሎ በጠላቶቹ በአይሁድ እጅ ወድቆ ተጐሰመ፤ ተንገላታ፤ በጥፊም ተመታ (ማቴ 27-27)፡፡ ጲላጦስ አሳልፎ ከሰጠው በኋላም አክሊለ ሦክ በራሱ ላይ አኑረው ቀይ ልብስ አልብሰው ‹‹የአይሁድ ንጉሥ ሆይ፣ ሰላም ለአንተ ይሁን›› እያሉ እየተሳለቁበት በጥፊ መትተውታል (ዮሐ 19-2-4)፡፡ አላወቁትም እንጂ እርሱ በመንግሥቱ ሽረት፣ በባሕርዩ ሞት የሌለበት የዘለዓለም አምላክ ነው፡፡

3.     ወሪቀ ምራቅ (ምራቅ መተፋት)

ርኩሳን አይሁድ በብርሃናዊው የክርስቶስ ፊት ላይ በሚያስጸይፍ ሁኔታ ምራቃቸውን እንደተፉበት የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ወሪቅ›› የሚለው ቃል ወረቀ ካለው ግእዛዊ ግሥ የተገኘ ነው፡፡ ትርጉሙም እንትፍ አለ፣ (ተፋ) ማለት ነው፡፡ በነቢዩ በኢሳይያስ መጽሐፍ (ምዕራፍ 5ዐ-6) ‹‹ፊቴንም ከውርደትና ከትፋት አልመለስኩም›› ተብሎ እንደተነገረ እየዘበቱበት ምራቃቸውን ተፉበት (ማቴ 27-29-3ዐ፤ ማር 15-19)፡፡ በኃጢአት የቆሸሸውን የሰውን ሕይወት ለማጥራት የመጣው ንጹሐ ባሕርይ አምላክ ተተፋበት፡፡ በሥራው ከገነት ተተፍቶ፤ ተንቆ፤ ተዋርዶ የነበረውን የሰውን ልጅ ለማዳን ኃጢአትን ይቅር የሚል እርሱ ጌታችን ያለ ኃጢአቱ ተተፋበት፤ ተናቀ፤ ተዋረደ፡፡ እንኳን በአምላክ ፊት በሰው ፊት እንኳን መትፋት እጅግ ያስነውራል፡፡ እርሱ ግን የኃጢአታችንን ነውር ከእኛ ሊያጠፋ ነውር የሆነውን ምራቅ ተቀበለ፡፡

4.     ሰትየ ሐሞት (መራራ ሐሞት መጠጣት)

ጌታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመልዕልተ መስቀል ሳለ ተጠማሁ ባለ ጊዜ መራራ ሐሞት መጠጣቱን የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ሰተየ›› ማለት ጠጣ ማለት ነው፡፡ ሐሞት የሚለውም አሞት ተብሎ በቁሙ ይተረጐማል፡፡ በመዝሙር 68 ቁጥር 21 ላይ ‹‹ለመብሌ ሐሞት ሰጡኝ፣ ለጥማቴም ሆምጣጤ አጠጡኝ›› ብሎ ነቢዩ ዳዊትን ትንቢት ያናገረ የነቢያት አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ የመጽሐፉ ቃል ይፈጸም ዘንድ ‹‹ተጠማሁ›› ባለ ጊዜ ሆምጣጤ ተሞልቶበት ተቀምጦ ከነበረው ዕቃ ሆምጣጤውን በሰፍነግ ሞልተው ወደ አፉ አቀረቡለት፡፡ ውኃ አጠጡኝ ቢላቸው በሐሞት የተደባለቀ የወይን ጠጅ ሊጠጣ አቀረቡለት፡፡ ቀምሶም ሊጠጣው አልወደደም (ማቴ 27-34)፡፡ ጌታችንም ሆምጣጤውን ከተቀበለ በኋላ ‹‹ተፈጸመ›› አለ፡፡ ራሱንም አዘንብሎ ነፍሱን አሳልፎ ሰጠ (ማቴ 27-48፤ ማር 15-36፤ ሉቃ 23-36፤ ዮሐ 19-29)፡፡

ቢጠጡት ለዘለዓለም የማያስጠማ ውኃ የሚሰጥ አምላክ፤ የተጠማችውን ነፍስ የሚያረካ ጌታ፤ ለዘለዓለም የሚፈልቅ የሕይወት ውኃ ምንጭ የሚያድል ፈጣሪ በተጠማ ጊዜ የፈጠረውን ውኃ እንኳን የሚያጠጣው የሚያቀምሰውም አላገኘም (ኢሳ 55-1)፡፡ አርባ ዓመት ሙሉ በቃዴስ በረሃ ኳትነው ለነበሩ አባቶቻቸው ከሰማይ መና አውርዶ የመገባቸው፤ ከአለት ላይ ውኃ አመንጭቶ ያጠጣቸው ክርስቶስ በተጠማ ጊዜ ቀዝቃዛ ውኃ ነፈጉት (ዘዳ 16-1-2ዐ፤ 1ቆሮ 1ዐ-3)፡፡ የዝናማት፤ የባሕርና የውቅያኖስ ጌታ በውኃ ጥም ተቃጠለ፡፡

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሲኦል በረሃ ወድቀው በሕይወት ውሃ ጥም የተቃጠሉትን ነፍሳት ለማርካት ሲል እርሱ ተጠማ፡፡ በኃጢአት ወድቀው፣ በበደል ረክሰው፣ በነፍሳቸው ተጐሳቁለው፣ መራራ መከራን የሚቀበሉትንና ምረረ ገሃነም አፉን ከፍቶ ሆዱን አስፍቶ የሚጠብቃቸውን ሁሉ ለማዳን መራራ ሐሞትን ቀመሰ፤ ሆምጣጣውንም ጠጣ፡፡ የመረረውን የሰው ልጆችን ሕይወት ለማጣፈጥ የመረረውን መጠጥ ተቀበለ፡፡

5.     ተቀሥፎ ዘባን (ጀርባን መገረፍ)

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጀርባው እስኪላጥ ያለ ርኅራኄ የመገረፉን ነገር የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ተቀሥፎ›› የሚለው ቃል ቀሠፈ- ገረፈ ካለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ነው፡፡ ‹‹ዘባን›› ደግሞ ጫንቃ፣ ትከሻ፣ ጀርባ ማለት ነው፡፡ ከላይ እንደተገለጠው የተገረፈ አይሰቀልም፡፡ የሚሰቀል ደግሞ አይገረፍም ነበር፡፡ ጲላጣስ ግን ኢየሱስ ክርስቶስን አስገረፈው፡፡ ከደሙ ንጹሕ ነኝ ብሎ ከታጠበ በኋላ ክርስቶስን ያለ ኃጢአቱ በመግረፍ ለአይሁድም አሳልፎ በመስጠት ‹‹ታጥቦ ጭቃ›› እንዲሉ የታጠበ እጁን መልሶ አቆሸሸው (ማቴ 27-28፤ ማር 15-15፤ ዮሐ19-1)፡፡

መድኃኒታችን መንፀፈ ደይን ወድቆ በእግረ አጋንንት ተጠቅጥቆ በእሳት አለንጋ የሚገረፈውን የሰው ልጅ ለማዳን ሲል ጀርባውን ለግርፋት ሰጠ፡፡ ሥጋው አልቆ አጥንቱ እስኪቆጠር ተገረፈ፡፡ አይሁድ አገረ ገዥያቸው ጲላጣስ ላቀረበላቸው ምርጫ ይፈታላቸው ዘንድ ነፍሳትን ከሲኦል የሚያወጣውን ክርስቶስን ሳይሆን ራሱን እንኳን ከምድራዊ ወህኒ ማውጣት ያልቻለውን ወንበዴውን በርባንን መረጡ፡፡ መገረፍ ይገባው የነበረ በርባን ተለቀቀ፡፡ በነቢዩ በኢሳይያስ ‹‹ጀርባዬን ለገራፊዎች፣ ጉንጬንም ለጠጉር ነጪዎች ሰጠሁ›› (በኢሳ 5ዐ-6) ተብሎ እንደተነገረ ጀርባውን ለገራፊዎች አሳልፎ ሰጠ፤ ጽሕሙንም ተነጨ፡፡ ይህ ሁሉ የሆነው የሰው ልጅ ከሚያድነው አምላክ ይልቅ የሚገርፈውንና የሚዘርፈውን ወንበዴ መርጦ ስለተገኘ ነው፡፡

6.     ተዐርቆተ ልብስ (ከልብስ መራቆት)

አምላካችን ኢየሱስ ክርስስቶስ ልብሱን መራቆቱን የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ተዐርቆተ›› ማለት ታረዘ፤ ተራቆተ ማለት ነው፡፡ ፀሐይና ከዋክብትን ብርሃን አልብሶ የፈጠረ አምላክ ተራቆተ፡፡ ጸጋውን ለዕሩቃን የሚያለብስ አምላክ ልብሱን ተገፍፎ ዕራቁቱን ቆመ፡፡ ጨለማን ለብሶ ጨለማን ተንተርሶ ይኖር የነበረውን ሰው መልሶ ብርሃን ያለብሰው ዘንድ የብርሃናት ጌታ፣ የጸጋ ሁሉ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ተገፈፈ፤ ተራቆተ፡፡

የሲኦል ወታደሮች የሆኑት አጋንንት የሰውን ልጅ ጸጋ ገፍፈውት ነበርና ጲላጦስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን አሳልፎ በሰጣቸው ሰዓት ወታደሮች ልብሱን ገፍፈውታል (ማቴ 27-27)፡፡ የሰው ልጅ ለቀረበለት ምርጫ የሰው ምላሽ ዘራፊው፤ ገራፊው ወንበዴ በርባን እንዲፈታለት ነበር፡፡ ‹‹አቅረብኩ ለከ እሳተ ወማየ፣ ደይ እዴከ ኅበ ዘፈቀድከ! እነሆ እሳትና ውኃን አቅርቤልሃለሁ፣ እጅህን ወደ ፈቀድከው ስደድ›› ሲባል የሰው ልጅ እጁን ወደ እሳት ሰደደ፡፡

7.     ርግዘተ ገቦ (ጎንን መወጋት)

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነፍሱን ለሞት አሳልፎ ከሰጠ በኋላ ጎኑን በስለታም ጦር መወጋቱን የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ርግዘት›› የሚለው ቃል ረገዘ- ወጋ ከተሰኘ የግእዝ ግሥ የወጣ ነው፡፡ ገቦ ማለት ደግሞ ጎን ማለት ነው፡፡ ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ አጠገብ፣ በግራና በቀኙ ሁለት ወንበዴዎች ተሰቅለው ነበር፡፡ ሥጋቸው በሰንበት በመስቀል ላይ እንዳይኖር ጭናቸው ተሰብሮ እንዲወርዱ አይሁድ ጲላጦስን በለመኑት መሠረት ጭፍሮቹ የሁለቱን ወንበዴዎች ጭን ጭናቸውን ከሰበሩ በኋላ ወደ ጌታችን ወደ ኢየሱስ ሲመጡ ፈጽሞ እንደሞተ አይተው ጭኑን አልሰበሩም፡፡ ነገር ግን ከጭፍሮቹ አንዱ ጎኑን በጦር ስለወጋው ወዲያው ከጎኑ ደምና ውኃ ፈሰሰ (ዮሐ 19-33)፡፡

አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን ድል ያደርገው ዘንድ ሞተ፤ የሰው ልጅ በዘለዓለማዊ ሞት ተይዞ ነበርና፡፡ ትልቁ ሞት በኃጢአት ምክንያት ከእግዚአብሔር መለየት ነው፡፡ በጌታችን ሞት ግን ሞት ራሱ ድል ተነሣ፡፡ የሞት መውጊያ በሆነ ኃጢአት የሞተውን ሰው ለማዳን ጎኑን በጦር ተወጋ፡፡ በሰው ልቡና ተተክሎ የነበረውን ኃጢአት ከነሥሩ ነቅሎ ስለጣለው ‹‹ሞት ሆይ መውጊያህ የት አለ?›› ተባለ፡፡ የሞት መውጊያው ኃጢአት ነበርና (1ቆሮ 15-54-55፤ ኢሳ 25-8፤ ሆሴ 13-14)፡፡

ከተወጋው የጌታችን ጎን ደምና ውኃ መፍሰሱም የእግዚአብሔርን ልጅነትና የዘለዓለምን ሕይወት አጥቶ የነበረው ሰው ልጅነቱና ሕይወቱ እንደተመለሰለት የሚያረጋግጥ ነው፡፡ ምክንያቱም ከጎኑ በፈሰሰው ውኃ ተጠምቆ ልጅነትን፣ ደሙንም ጠጥቶ የዘለዓለም ሕይወትን ያገኛልና (ዮሐ 3-5፤ ዮሐ 6-54)፡፡

8.     ተአሥሮተ ድኅሪት (ወደ ኋላ መታሠር)

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁለት እጆቹን ወደኋላ የፊጥኝ መታሠሩን የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ተአሥሮት›› የሚለው ቃል አሠረ (ሲነበብ ይላላል) ከሚለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም አሠረ ማለት ነው፡፡ ‹‹ድኅሪት›› የሚለው ቃል ደግሞ ተድኅረ- ወደኋላ አለ ከሚለው ግሥ የወጣ ነው፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጊዜው በደረሰ ሰዓት ራሱን ለአይሁድ አሳልፎ በሰጠባት በዚያች ዕለትና ሰዓት ሻለቃውና ጭፍሮቹ የአይሁድም ሎሌዎች እጁን የኋሊት አሥረው መሬት ለመሬት ጎትተውታል፡፡ አፍገምግመውታል (ዮሐ 18-12)፡፡

በኃጢአት ሰንሰለት የኋሊት ታሥሮ ጠላት ዲያብሎስ የሚያፍገመግመውን የሰው ልጅ ለማዳን፣ ሰውንም ከኃጢአት እሥራት ይፈታ ዘንድ ሲል መድኃኔዓለም ክርስቶስ በጠላቶቹ በአይሁድ እጅ የኋሊት ታሠረ፡፡

9.     አምሥቱ ቅንዋተ መስቀል

መድኃኒታችን በመስቀል ላይ የተቸነከረባቸውን ጠንካራ የብረት ችንካሮች (ምስማሮች) የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ቅንዋት›› የሚለው ቃል ቀነወ- ቸነከረ ከሚለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ነው፡፡ መስቀል ማለት ደግሞ ዝም ብሎ የቆመ ግንድ ሳይሆን አሁን በየሥፍራው እንደምናየው ምልክት የተመሳቀለ እንጨት ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተቸነከረባቸው አምስቱ ችንካሮች ሳዶር፣ አላዶር፣ ዳናት፣ አዴራ፤ ሮዳስ ይባላሉ፡፡ እነዚህም የአምሥቱ አዕማደ ምሥጢራት ምሳሌዎች መሆናቸውን አበው ያስተምራሉ፡፡

ሐዋርያው ቶማስ ከትንሣኤ በኋላ ወንድሞቹ ሐዋርያት ስለ ትንሣኤው በነገሩት ጊዜ ‹‹የችንካሩን ምልክት በዓይኖቼ ካላየሁ፣ ጣቴንም በችንካሩ ምልክት ካላስገሁ፣ በእጄም የተወጋውን ጎኑን ካልዳሰስኩ አላምንም›› ማለቱ በብረት ቀኖት በመቸንከሩ ነበር (ዮሐ 2ዐ-25)፡፡ መድኃኒታችን በኃጢአት ቀኖት (ምስማር) ተይዞ የነበረውን ሰው ለማዳን በብረት ቀኖት ተቸነከረ፡፡

እንግዲህ አሥራ ሦስቱ ሕማማተ መስቀል የሚባሉት እነዚህ ናቸው፡፡ ድሀ ያይደለ ጌታ፤ ፍጡር ያይደለ የፈጠረውን ሥጋ ገንዘብ ያደረገ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጅ ብሎ ተናቀ፡፡ የሕማም ሰው፤ ደዌንም የሚያውቅ ሆነ፡፡ በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ በእውነት ደዌያችንን ተቀበለ፡፡ ሕማማችንንም ተሸከመ፡፡ ይህም የሰውን ልጅ ለማዳን ማለትም እኛን ከደዌ ሥጋ ከደዌ ነፍስ ይፈውሰንና ከሕማመ ሥጋ ከሕማመ ነፍስ ሥቃይ ያሳርፈን ዘንድ ነው፡፡ ቁስለ ኃጢአታችንን ያደርቅልን ዘንድ ስለ መተላለፋችን ቆሰለ፡፡ በእርሱ ቁስል እኛ ተፈወስን፡፡ በደላችንን ይደመስስ ዘንድ ስለ በደላችን ደቀቀ፡፡ ሊያረጋጋን ተጨነቀ፡፡ ሊያሣርፈን ተሠቃየ፡፡ አፉንም አልከፈተም፡፡

እግዚአብሔር የመሥዋዕቱ በግ ኢየሱስ ክርስቶስ ለመታረድ እንደሚነዳ ጠቦት በሸላቾቹም ፊት ዝም እንደሚል በግ እንዲሁ አፉን አልከፈተም፡፡ መልካምን እንጂ ግፍን አላደረገም ነበር፡፡ ልብንና ኩላሊትን የሚመረምር አምላክ ወሰብእ ወልድ ዋህድ ኢየሱስ ክርስቶስ በጲላጦስ በተመረመረ ጊዜ በአፉም ተንኮል አልተገኘበትም፡፡ በፈቃዱ ነፍሱን ስለ እኛ መሥዋእት አደረገ፡፡ ፋሲካችን ክርስቶስ በመስቀል ላይ ሥጋውን ቆረሰልን፣ ደሙንም አፈሰሰልን (ኢሳ. 53-1-13፤ ዮሐ. 10-18፤ ዮሐ. 19-30፤ 1ኛቆሮ. 5-7)፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስም ‹‹ተንኰልም በአፉ አልተገኘበትም ሲሰድቡት መልሶ አልተሳደበም መከራንም ሲቀበል አልዛተም ነገር ግን በጽድቅ ለሚፈረደው ራሱን አሳልፎ ሰጠ፡፡›› ለኃጢአት ሞትን ለጽድቅ እንድንኖር እርሱ ራሱ በሥጋው ኃጢአታችንን ተሸከመ፡፡ በመገረፉ ቁስል ተፈወሳችሁ ብሏል (1ጴጥ.22-2-25)፡፡ ክርስቶስ የሞተልን ለጽድቅ ሞተን ለኃጢአት እንድንኖር አልነበረም፤ የኃጢአት ኑሮ እንዲያከትምልን እንጂ፡፡

እንግዲህ የእኛ ሕያውነትስ ለጽድቅ ይሆን ወይስ ለኃጢአት ዛሬ ሕይወታችንን መለስ ብለን ልናጤነው ሥጋዊ ፍላጎታችንንና የዓይን አምሮታችንን ክደን ነፍሳችንን ለማዳን መከራ መስቀሉን ተሸክመን ሕማማቱን እያሰብን ፈጣሪአችን ክርስቶስን ልንከተለው ይገባን ነበር (ማቴ.16-24)፡፡ እንደ ቅዱስ ጳውሎስ ትምክህታችን መስቀሉ ማለትም በመስቀሉ ላይ የተፈፀመው ቤዛነት መሆን አለበት፡፡

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጽኑ መከራ ማለትም በመከራ ሥጋ ላይ መከራ ነፍስ፣ በሞተ ሥጋ ላይ ሞተ ነፍስ፣ በርደተ መቃብር ላይ ርደተ ገሃነም የተፈረደበትን ሰው ለማዳን ጽኑ መከራ ተቀበለ፡፡ የለበሰው ሥጋ መከራ የተፈረደበት ነበርና በዕፅ ምክንያት ወደ ዓለም የገባውን ኃጢአት ለማስወገድ በዕፀ መስቀል ላይ ተሰቀለ፡፡ የበለሲቱ ደም ፈስሷልና ክርስቶስ ደሙን አፈሰሰ፡፡ አዳም እጁን ዘርግቶ የበለሲቱን ደም ለማፍሰስ ደሙን አፈሰሰ፡፡ አዳም እጁን ዘርግቶ የበለሲቱን ደም ለማፍሰስ በእግሮቹ ወደዚያ ተጓዘ፡፡ ክርስቶስ ግን በእግሮቹ ወደ ቀራንዮ ተጉዞ እጆቹን ለቀኖት ዘርግቶ የራሱን ደም አፈሰሰ፡፡ በችንካርም ላይ ቆመ፡፡ አዳም የበለሲቱን ፍሬ ወደ አፉ አሰገብቶ አጣጣመ፡፡ ክርስቶስ ግን መራራ ሐሞትን ቀመሰ፡፡ ሆምጣጤንም ጠጣ፡፡ አዳም የብርሃን ልብሱን ተገፍፎ ራቁቱን ቀረ፣ በበለስ ቅጠል ተሸፈነ፡፡ ክርስቶስ ግን ልብሱን ተገፍፎ ዕራቁቱን ተሰቀለ፡፡ ፀሐይም በመጨለሟ በጨለማ መጋረጃነት ተሸፈነ፡፡ ይልቁንም አዳም የተጎዳው በነፍሱ ነውና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሕይወቱን ክሶ ታረቀው፣ ከራሱም ጋር አስታረቀው፡፡

ዛሬ ግን ክርስቶስ አሥራ ሦስቱን ሕማማተ መስቀል በትዕግሥት ተቀብሎ ኃጢአታችንን ካራገፈልን በኋላ በኃጢአት ሸክም ጎብጠን ተገኘን፡፡ ‹‹እናንተ ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ ወደ እኔ ኑ፣ እኔም አሳርፋችኋለሁ›› በሚለው አምላካዊ ቃል ብንጠራም ጆሮ ዳባ ልበስ ብለናል፡፡ በመስቀሉ ደም ሰላም ሆኖልን ሳለ በጦርነት ውስጥ ተዘፍቀናል፡፡ ከታረቀን በኋላ ተጣላን፡፡ ከእርግማን ሲዋጀንም ዳግመኛ ከእርግማን በታች ወደቅን፡፡ የመስቀሉ ነገር በመስቀል ላይ የተፈጸመው ቤዛነት ሥጋ ወደሙን መቀበል መስቀል መሳለም በመስቀል ማማተብ የመስቀል ምልክት መያዝም ሞኝነት ሆነብን፡፡ በዚህ በመጨረሻው ዘመን የመስቀል ጠላቶች ሆነን ተመላለስን ሆዳችንን (ሥጋችንን) አመለክን፡፡ ነውር መሥራትን እንደክብር ቆጠርነው፡፡ ለሰማያዊ ክብር ባለቤትነት ከሞተልን በኋላ አሳባችን ምድራዊ ሆኖ ተገኘ (ማቴ.11-28፡፡1ቆሮ.1-18፡፡ ቆላ.1-18)፡፡

ዛሬም በእኛ እጅ ክርስቶስን የምናሳዝንበትንና የምናስቀይምበት የኃጢአትና የበደል መቃ አለ፡፡ ወገኖቻችንን በግፍ ቀንበር የምናደቅቃቸው፣ በግፍ በትር የምንቀጠቅጣቸው ከሆነ ይኸም ክርስቶስ ራሱን የተቀጠቀጠበት መቃ ነው፡፡ ምክንያቱም በታናናሾቻችን ላይ የምንፈጸመው ሁሉ በእሱ ላይ እንደተፈጸመ ይቆጠራልና፤ ሳውል ክርስቲያኖችን ባሳደደ ጊዜ ክርስቶስ በሰማይ ሆኖ ‹‹ለምን ታሳድደኛለህ›› ማለቱ ለዚህ ነው (የሐዋ.9-1-30)፡፡

ትናንት ክፉዎች አይሁድ በጥፊ እንደመቱት እኛም በዕደ ልቡናችን በክህደት ጥፊ እየመታነው ነው፡፡ እንደ አይሁድ እጆቻችንን ለበደል እየዘረጋን ነው፡፡ በጥፊ የመታህ ማነው? እወቅ እያሉ እንዳፌዙበት እኛም እግዚአብሔር እንደማያውቅ አድርገን በምንሠራው ሥራ እየቀለድንበት ነው፡፡ እግዚአብሔር ካለ ለምን እንዲህ አያደርግም እያልን እያፌዝንበት ነው፡፡ ከኃጢአት ለመመለስ በደልን ለማራቅ ሳንወስን በፊቱ መንበርከክ ፌዝ ነው፡፡

ምን ያደርገኛል? ማንስ ምን ሆነ? በሚል ደካማ አስተሳሰብ በእግዚአብሔር ፊት የማይገባ ሥራ መሥራት እንደ አይሁድ በፊቱ ላይ መትፋት ነው፡፡ አይሁድ ቢንቁት አይደል በፊቱ ላይ የተፉት? እኛም ብንንቀው ነው በፊቱ ኃጢአት የምንሠራው፤ ምራቅ አስጸያፊ እንደሆነ ኃጢአትም አስጸያፊ ነው፡፡ እነዚያ ነውራቸውን እንደ መልካም እንዳዩት እኛም ነውር ኃጢአታችን መልካም ይመስለናል፡፡

ተጠማሁ ባለ ጊዜ ለመብሉ ሐሞት ለመጠጡ ሆምጣጤ አቀረቡለት፡፡ ትናንትና ዛሬ ለዘላለም ሕያው የሆነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዛሬም ጽድቅን ተርቦና ተጠምቶ ሳለ ምንድን ነው ያቀረብንለት? ሕይወታችን ጣፋጭ ነው? ወይስ መራራ? ዛሬ ያቀረብንለት መጠጥ የኃጢአትና የበደል መራራ ሆምጣጣ መጠጥን ነው፡፡ ይኽም የእግዚአብሔር ወዳጆች አለመሆናችንን ያሳያል፡፡ ምክንያቱም ማንም ቢሆን ለወዳጁ የሚያቀርበው መራራውን ሳይሆን ጣፋጩን ነውና፤ መራራውን አሞት ቀምሶ የተወ አምላክ እኛንም ዓይቶ መርምሮ መራሮች ሆነን ካገኘን ለምረረ ገሃነም ይተወናል፡፡

የክፋት የምቀኝነት የግብዝነት የትዕቢት የአመንዝራነት አለንጋ በእጃችን ካለ ይኽም ክርስቶስ የተገረፈበት አለንጋ ነው፡፡ ክርስቶስን ካሳዘንነው ካስቆጣነው በክፉ ሥራችን በሐዘን በንዴት በቁጣ አለንጋ ገረፍነው ማለት ነው፡፡ ወገኖቻችንን የምንገርፍበትም የግፍ አለንጋ በእጃችን እስካለ ድረስ የዛሬዎቹ አይሁዳውያን እኛ ነን፡፡ እንደ ጲላጦስ ንጹሖች ነን እያልን እየተገዘትን ወገኖቻችንን በግፍ አለንጋ የምንገርፍ ዛሬም አለን፡፡

ምርጫችንስ ወንበዴው በርባን ነው ወይስ ጻድቁ ክርስቶስ ነው? ጦረኛውን በርባንን ነው ወይስ ሰላማዊውን ክርስቶስን ነው? የወገኖቹን ደም የሚያፈሰውን በርባንን ነው ወይስ ስለ ወገኖቹ ደሙን ያፈሰሰውን ክርስቶስን ነው? ዛሬም በዓለማችን ብዙ በርባኖች አሉ፡፡ የእኛም ምርጫ በርባኖችን ሆኗል፡፡ ረቂቁን በርባን ዲያቢሎስን መርጠናል፡፡ ክርስቶስን አስወግደው እንዳሉ ከልባችን ክርስቶስን አስወግደነዋል፡፡ ከሕይወታችን ለይተነዋል፡፡ ክርስቶስ የሞተለትን ሰውነት ከጽድቅ አራቁተን ከተገኘን ክርስቶስን ገፈፍነው ማለት ነው፡፡ የበላነው ሥጋው የጠጣነው ደሙ በውስጣችን አለና፡፡

ዛሬ የክርስቶስን የፈራጅነትና የሁሉን ቻይነት ሥልጣን ገፍፈው አማላጅ የሚሉት አሉ፡፡ የፈጣሪነቱንም ክብር ገፍፈው ፍጡርም ብለውታል፡፡ እሱ ግን ፈራጅ እንጂ አማላጅ ፈጣሪ እንጂ ፍጡር አይደለም፡፡ በተዋሕዶ የከበረ የአብ ልጅ የማርያም ልጅ ነው፡፡ ከተዋሕዶ በኋላ ሁለትነት የለም፡፡ አንድ አካል አንድ ባሕርይ ነው፡፡ ለክርስቶስ የሚገባውን ክብር አለመስጠትም ልብሱን እንደ መግፈፍ ይቆጠራል፡፡

ከጭፍሮች አንዱ በስለታም ጦር ጎኑን እንደወጋው በክህደትና በጥርጥር ጦር እየወጋነው ነው፡፡ በኃጢአት የቆሸሸው በበደል የረከሰው ሕይወታችን ለክርስቶስ የጎን ውጋቱ ነው፡፡ የክፉ ምግባራቸው ተባባሪ ሆነን የጭካኔ ጦር ዛሬም በእጃችን አለ፡፡ በጦር ከተወጋ በነገር የተወጋ እንዲሉ በነገር ጦር ስንቱን አቁስለናል? የትዕቢት ጦር የመዘዝን የለንም? በእኛ ምክንያት በሐዘን ጦር ተወግተው የወደቁ ብዙዎች ናቸው፡፡ ከክርስቶስ ጎን ደምና ውኃ እንደፈሰሰ ደም እንባ የሚያለቅሱ ክርስቶሳውያን ዛሬም አሉ፡፡

በክፉ ሥራችን የእግዚአብሔር ምሕረት ወደ መዓት፣ ትዕግሥቱ ወደ ቁጣ እንዲለወጥ በማድረግ ለሰላም፣ ለፍቅር፣ ለምሕረት፣ ለረድኤት፣ ለበረከት፣ ለቸርነት የተዘረጋው ቅዱስ እጁ እንዲታጠፍ ካደረግን፤ እጁን የኋሊት ጠፍሮ እንደማሰር ነው፡፡ እሱ እጁን ዘርግቶ እንካችሁ ተቀበሉ ሲለን አንቀበልም ማለት እጁን የኋሊት ማሰር ነው፡፡ የዛሬው የክርስቶስ ሥቃይ ይህ ነው፡፡

አስማተኝነቱ፣ ሴሰኝነቱ፣ ነፍሰ ገዳይነቱ፣ አምልኮተ ጣዖቱ፣ ሐሰተኝነቱ፣ ይህ የዘመናችን ችንካር ነው፡፡ ትዕቢቱ፣ ስስቱ፣ ገንዘብ መውደዱ፣ ይህም ችንካር ነው፡፡ ክርስቶስ የተንገላታለት፣ ሥጋውን የቆረሰለትና ደሙን ያፈሰሰለት፣ ሕይወቱን የካሰለት ሕዝብ እንዲህ ሆኖ ሲያገኘው እጁጉን ያዝናል፡፡ እንደመስቀሉ ችንካር ያቆስለዋል፡፡

በሐዋርያት ላይ መንፈስ ቅዱስ በወረደላቸው ዕለት የቅዱስ ጴጥሮስን ስብከት የሰሙት ሕዝብ ‹‹እንግዲህ ምን እናድርግ?›› እንዳሉ እኛም አሁኑኑ ‹‹ምን እናድርግ?›› ልንል ይገባናል፡፡ የምናደርገውም ነገር ቀላል ነው፡፡ ንስሐ መግባት፣ ከኃጢአት መመለስ፣ ከበደል መራቅ፣ ወደ ቀራንዮ ማቅናት፣ ወደ መስቀሉ መመልከት ነው፡፡ ጌታ የሚወደው ደቀ መዝሙር ዮሐንስ በመስቀሉ ፊት ቆሞ እንደተገኘ የእናት አማላጅ ቅድስት ድንግል ማርያምን እንዳገኘ፣ እኛም እንደተወደዱ ልጆች ከመስቀሉ ፊት አንጥፋ፡፡ ‹‹እነኋት እናትህ›› ተብላ በዮሐንስ በኩል የተሰጠችንን የአደራ እናት ይዘን እንገኝ፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ጌታን ከእናቱ ጋር ያገኘው በቀራንዮ ነው፡፡፡ ስለዚህ እኛም ወደ ቀራንዮ እንጓዝ፡፡ ጌታን ከእናቱ ጋር እንድናገኝ፤ አባትም እናትም እንዲኖረን፣ የዛሬዋ ቀራንዮ ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ዕለት ዕለት አማናዊው የክርስቶስ ሥጋ ይቆረስባታል፡፡ ደሙ ይፈስባታል፡፡ በክርስቶስ ደም የከበረው መስቀል በክብር አለ፡፡ የበደል ግድግዳ የፈረሰበት ጥል የተባለ ዲያቢሎስ የተገደለበት ነውና፡፡ ዛሬም ሰላም ያገኘንበትን መስቀል እናከብረዋለን እንሳለመዋለን፡፡ በመስቀል ምልክትም ጥንተ ጠላታችንን ዲያቢሎስን እንቀጠቅጥበታለን፡፡ ተቃጠልኩ አረርኩ እናሰኝበታለን፡፡ በሲዖል ሲያቃጥለን የነበረውን ጠላት ዛሬ ተራችንን በክርስቶስ መስቀል እናቃጥለዋለን፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ በቀራንዮ ያገኛትን ዘለዓለማዊት ድንግል ቅድስት ማርያምን ከተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እናገኛታለን፡፡ የአማላጅነቷ ተጠቃሚዎች እንሆናለን፡፡ ጌታ በመጨረሻው ሰዓት በመስቀል ላይ ሆኖ እንደ ኑዛዜ ቢሉ ወይም እንደ አደራ ለሚወደው ደቀ መዝሙሩ ለዮሐንስ በዘለዓለማዊ ቃሉ ‹‹እነኋት እናትህ›› እንዳለው ዛሬም መሠረቷም ጉልላቷም ክርስቶስ የሆነ ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እያንዳንዱን ክርስቲያን በዘለዓለማዊው የጌታ ቃል ‹‹እነኋት እናትህ›› ትለዋለች፡፡ የሚያስፈልገው ነገር ቢኖር ዮሐንስን ሆኖ መስቀሉ ሥር መገኘት ነው፡፡ ዮሐንስ የጌታን ቃል አክብሮ እናቴ ብሎ ወደ ቤቱ እንዳስገባት እኛም እናቴ ብለን ቤት ወደሚባል ልባችን ማስገባት ይኸም የክርስቶስን የኑዛዜ ቃል መጠበቅ የአደራ ቃሉን ማክበር ነው፡፡ እሱ ‹‹የሚወደኝ ቢኖር ቃሌን ይጠብቃል›› እንዳለ እውነት የምንወደው ከሆነ ቃሉን እንጠብቅ (ዮሐ.14÷23)፡፡

አይሁድ ክርስቶስን እንደጠሉት እኛም አንጥላው፡፡ እውነተኛ መብል የክርስቶስ ሥጋ እውነተኛ መጠጥ የክርስቶስ ደም መጥላት በየምክንያቱም ከእርሱ መራቅ ክርስቶስን መጥላት ነው፡፡ መጨነቅ መጠበብ የእንስሳት ሥጋ እና የዓሣ ሥጋ ቀረብኝ ብሎ ሳይሆን የቀራንዮው በግ የኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋና ደም ለምን ይቅርብኝ ብሎ ነው፡፡ አይሁድ ክርስቶስን አልተቀበሉትም፤ አራቁት (ሰቀሉት) እንጂ፡፡ እኛም ሥጋውና ደሙን አልተቀበልንም፤ አራቅነው እንጁ፡፡ ስለዚህ ወደ ሕይወት መድኃኒት እንቅረብ፡፡

በዚህ የተቀደሰው ሳምንት ይህንን የጌታን ውለታና የድኅነት ሥራ እናስተውል፡፡


ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡